የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ የኢትዮጵያ የማምረት አቅም ማደጉን ያየንበት ነው (የተለያዩ ሀገራት ዲፕሎማቶች )

ሚያዚያ 28/2017(ኢሚ) የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ የኢትዮጵያ የማምረት አቅም ማደጉን ያየንበት ነው ሲሉ ተቀማጭነታቸውን አዲስ አበባ ያደረጉ የተለያዩ ሀገራት ዲፕሎማቶች ተናገሩ።

ኢትዮጵያ በትክክለኛው የእድገት ጎዳና ላይ መሆኗን መገንዘባቸውንም ዲፕሎማቶቹ ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ ሚያዚያ 25 በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በይፋ ተመርቆ መከፈቱ ይታወቃል።

እየተካሄደ በሚገኘው ኤክስፖ ላይ 288 አምራቾች ምርታቸውን አቅርበው በማስጎብኘት ላይ ሲሆኑ በነገው እለትም የሚጠናቀቅ ይሆናል።

ተቀማጭነታቸውን አዲስ አበባ ያደረጉ የተለያዩ ሀገራት ዲፕሎማቶች በኤክስፖው የቀረቡ ምርቶችን ዛሬ ጎብኝተዋል።

ከጎብኚዎቹ መካከል በኢትዮጵያ የፖርቹጋል አምባሳደር ሊዊሳ ፍራጎሶ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ኤክስፖው ኢትዮጵያ ወደ ኢንዱስትሪ ሽግግር ለማድረግ እየተገበረቻቸው ያሉ ኢኒሼቲቮች ውጤታማ መሆናቸውን ያየሁበት ነው ብለዋል።

በኤክስፖው ላይ የቀረቡ የምርቶች ስብጥር እንዲሁም ብዛት የኢትዮጵያ የማምረት አቅም እያደገ መምጣቱን የሚያሳይ መሆኑንም ገልጸዋል።

ፖርቹጋል ከኢትዮጵያ ጋር ትብብሯን ማጠናከር እንደምትፈልግ የገለጹት አምባሳደር ሊዊሳ የፖርቹጋል ኩባንያዎች ከኢትዮጵያ ኩባንያዎች ጋር ይበልጥ ተቀራርበው እንዲሰሩ ፍላጎት አለን ብለዋል።

ይህንንም እውን ለማድረግ በጋራ እንሰራለን ነው ያሉት።

በሀገራቱ መካከል ያለው የንግድ ልውውጥም ከፍ ወዳለ ደረጃ እንዲሸጋገር የሁለትዮሽ ትብብር ይበልጥ ሊጠናከር እንደሚገባም አመልክተዋል።

በኢትዮጵያ የማልታ አምባሳደር ሮላንድ ሚካሌፍ በበኩላቸው ኤክስፖው በኢትዮጵያ ያሉ ዘርፈ ብዙ ለውጦች በተግባር የታየበት መሆኑን ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ አምራቾች የኢትዮጵያን ብልጽግና ለማሳካት ቁርጠኛ መሆናቸውን ያረጋገጥኩበት ኤክስፖ ነው ሲሉም ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ እድገት ቀጣይነት ያለው መሆኑንም መገንዘብ መቻላቸውን ተናግረዋል።

በኢትዮጵያ የሱዳን ሪፐብሊክ ምክትል አምባሳደር ኤልሀፊዝ ኢሳ አብደላ፤ የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ አብዮት ለሁላችንም ምሳሌ የሚሆን ነው ብለዋል።

ሙሉ በሙሉ የሀገር ውስጥ ምርቶች የቀረቡበት ግዙፍ ኤክስፖ መዘጋጀቱም ኢትዮጵያ ትክክለኛ የእድገት ጉዞ ላይ መሆኗን አመላካች መሆኑን ተናግረዋል።

#ኢትዮጵያ_ታምርት

#እኛም_እንሸምት

Share this Post