ተልዕኮ

አሰራርን ግልፅ፣ ተደራሽና ውድድር የሰፈነበት እንዲሆን በማድረግ፣ ለባለሃብቱ የላቀ አገልግሎትና ድጋፍ በመስጠት፤ የዘርፉን የሰው ሀብትና የቴክኖሎጂ አቅም በማሳደግ እና ውጤታማ የአሠራር ስርዓት በመዘርጋት የአምራች ኢንዱስትሪውን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ፤

ራዕይ

በ2022 የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ዘርፍ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ ሆኖ ማየት፤

ዋና እሴቶች

  • በአሳታፊነት፣ በግልፅነትና በተጠያቂነት ማገልገል፣
  • ለደንበኛ እርካታ ቅድሚያ ትኩረት መስጠት፣
  • ኪራይ ሰብሳቢነትን መታገል፣
  • በጋራ ተባብሮ የመስራት ባህልን ማሳደግ፣
  • ለባለሀብቱ ስኬት መትጋት፣
  • ሁልጊዜም ለመማርና ለለውጥ ዝግጁ መሆን፤
  • ለፈጣን የቴክኖሎጂ ሽግግርና ተጠቃሚነት መስራት፣
  • ለአካባቢ ደህንነትና እንክብካቤ መቆም፣
  • በቅንጅት መስራት፤

ተግባራት እና ኃላፊነቶች

  • የኢንዱስትሪ በተለይም የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ልማትንና ተወዳዳሪነትን በቀጣይነት የሚያረጋግጡ ፖሊሲዎችን፣ ስትራቴጂዎችን፣ ፕሮግራሞችን እና ሕጎችን ያመነጫል፣ ለአፈጻጸሙ ከሀገራዊ የልማት አቅጣጫ ጋር የተጣጣመ ዝርዝር መርሀ-ግብር ያዘጋጃል፤ በሚመለከተው አካል ሲጸድቅም ተግባራዊ ያደርጋል፤
  • በኢንዱስትሪ በተለይም በማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ዘርፍ የግል ዘርፉን ተሳትፎና ሚና ለማሳደግ የሚያስችል ሥርዓት ይዘረጋል፣ ለአፈጻጸሙ ምቹ ሁኔታን ይፈጥራል፤
  • በኢንዱስትሪ በተለይም ማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ልማት ትኩረት የሚሠጣቸውን ጨርቃ ጨርቅ፣ ቆዳ እና የምግብና መጠጥ ኢንዱስትሪዎችና የመሳሰሉት ንዑስ ዘርፎች ካላቸው አንጻራዊ ጠቀሜታና እምቅ አቅም አኳያ ይለያል፤ ለአፈጻጸሙ ዝርዝር ከሀገራዊ የልማት አቅጣጫ ጋር የተጣጣመ መርሀ-ግብር ያዘጋጃል፤ በሚመለከተው አካል ሲጸድቅም ተግባራዊ ያደርጋል፤
  • በዘርፉ ምርምርና ጥናት የሚያካሂዱ አካላትን አስፈላጊውን ድጋፍ በማድረግ የኢንዱስትሪዎችን፣ የኢንቨስትመንት እና የማኑፋክቸሪንግ አቅምና ተወዳዳሪነትን እንዲያድግ ያደርጋል፤
  • በኢንቨስትመንት ሕግ መሠረት የሀገር ውስጥ እና የውጭ ባለሃብቶች በማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ዘርፍ ኢንቨስትመንት የሚሳተፉበትን ሁኔታዎች ያመቻቻል፤ በሥሩ ያሉ ተጠሪ ተቋማት በዋናነት ለሀገር ውስጥ ባለሀብቶች ድጋፍ እንዲሰጡ ለማድረግ ተገቢውን ሥርዓት ይዘረጋል፣ ያስፈጽማል፤
  • የኢንዱስትሪ በተለይም የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ዘርፍ ልማትን ለማሳደግ የሚያስችሉ ተግባራትን፤ የምርጥ ተሞክሮ መቀመር፣ እና አጠቃላይ የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ልማት አቅም ግንባታ ሥራዎችን ይሰራል፤
  • የኢንዱስትሪ በተለይም የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ዘርፍ ልማትና ምርታማነትን ለማሳደግ ኢንዱስትሪዎች የኤክስቴሽን አገልግሎት፣ የቴክኖሎጂ፣ የግብዓትና የግብይት እንዲሁም በአመራረት ረገድ ድጋፍ እንዲያገኙ ያደርጋል፤ ውጤታማነታቸውንም ያረጋግጣል፤
  • የኢንዱስትሪ በተለይም የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ምርቶች የጥራት ደረጃቸውን የጠበቁ፣ በዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ የአቅም ግንባታ፣ የምርምርና ስርጸት ሥራዎች እንዲከናወኑ ሥርዓት ይዘረጋል፣ ተግባራዊነቱን ይከታተላል፤
  • ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመቀናጀት ለኢንዱስትሪ በተለይም ለማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ዘርፍ አስፈላጊ የሆነው የሰው ኃይል ፍላጎት እና አስተማማኝ ግብዓት ለማሟላት የሚቻልበትን ስልት ይቀይሳል፤ ከሚመለከተው ዘርፍና አካላት ጋር በመሥራት የኢንዱስትሪ ግብዓት አቅርቦት ትስስር ሥርዓት እንዲዘረጋ ሁኔታዎችን ያመቻቻል፤ ተግባራዊ ያደርጋል፤
  • ለዘርፉ እድገት ከሚመለከታቸው የፌደራልና የክልል አካላት ጋር በቅንጅት ይሠራል፣ ለዘርፉ አሳታፊና ዘላቂ መዋቅራዊ ለውጥ ስለሚመጣበት ሁኔታ ስልቶችን ይነድፋል፣ ተግባራዊ የሚሆኑበትን ሥርዓት ይዘረጋል፤
  • ለማዕድን ሚኒስቴር ከተሰጡ ሥልጣንና ተግባራት ውጪ ያሉ ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታቸው ጉልህ የሆኑ የኢንዱስትሪ ገቢ ምርቶች በሀገር ውስጥ ምርቶች እንዲተኩ ድጋፍ ያደርጋል፤
  • በአነስተኛ፣ በመካከለኛና በከፍተኛ የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪዎች መካከል የተቀናጀ ትስስር እንዲፈጠርና ስኬታማ ሽግግሮች እንዲከናወኑ የሚያስችሉ ፖሊሲዎች፣ ስትራቴጂዎች እና የአሠራር ሥርዓቶችን ይዘረጋል፤
  • የአነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞችን ውጤታማ እንዲሆኑ የማትጊያ ስልት ይቀይሳል፣ ድጋፍ ያደርጋል፤
  • የኢንዱስትሪ በተለይም የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪዎች በአካባቢ ጥበቃ የተቀመጡ መስፈርቶችን እንዲያሟሉ ድጋፍ ያደርጋል፤
  • የኢንዱስትሪ፣ የዘርፉ እና የሙያ ማህበራት እንዲቋቋሙ ያበረታተል፣ የተቋቋሙትንም እንዲበረታቱ ያደርጋል፡፡
  • በሥራ ላይ ባሉ ሌሎች ሕጎች ለንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ተሰጥተው የነበሩ ኢንዱስትሪን የሚመለከቱ ሥልጣንና ተግባራት በዚህ አዋጅ ለተቋቋመው ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ተሰጥተዋል።